Wednesday, September 16, 2015

አምሮቴ

ዘመን አልፎ ዘመን ሲተካ 
ምድር ስታጌጥ አድማስ ሲፈካ
ከሚገዳደር ያንቺን ሕላዌ
ዘገር ከሚሰብቅ ከክፉ ደዌ
ከዘውጌ ልምሻ ሥርየት አግኝተሽ 
የፍትሕ ጸበል ቡራኬ ጠጥተሽ
በሕዝብሽ ኅብር ተውበሽ ፈክተሽ
በዓለት ላይ ቁሞ ያንድነት ካስማ
እናፍቃለሁ ደግ ነገር ላይ፣በጎ ልሰማ
ከፍ ብለሽ ላይሽ በክብር ማማ፤ 
የፈጠረቀሽ-ክፉ ፃረ ሞት-ራሱ ታንቆ
ሕያው እስትንፋስ ከከርስሽ ፈልቆ
ሥርየት ስታገኝ ህልም አልማለሁ 
ጧቱ እንዲያምርልሽ ሰርክ እመኛለሁ፡፡ 
መጣሁ ሲል ዘመን-ልቤ ይጎናል-ተስፋ ያንቀኛል
ትንሣኤ አግኝተሽ-ክፉ ቀን አልፎ-ማየት ያምረኛል፡፡
ዘር ሳይዘራ-ሙቶ እንዲነሣ-ሳይኮተኮት ውኃ ሳይጠጣ
ከጥላቻ ሥር-ከጠብ አዝመራ-ማየት ያምረኛል መሲህ ሲወጣ
የሚያስከብርሽ-ውርደት ዝቅታን-አሻፈረኝ ባይ

ጀግና ያምረኛል-ለሐቅ የሚሞት-ባንቺ ሰማይ ላይ፤
ከአሮጌው ጋራ ክፉን የሚሸኝ-ኅብርን የሚያዜም-ያንድነት አቡን
ኢትዮጵያን የሚል-መንገድ ጠራጊ-አርቆ ዓላሚ የሚበጀንን 
ከአይመክኔ ማሕፀን-ከለሙ ማሳሽ-ከደጅሽ ፈልቆ
ውድቀትሽን ሽቶ-ጉድጓድ የማሰን-ጅስሙን አድቅቆ
ማየት ያምረኛል-ምድርሽ በፍትሕ-በሐቅ ደምቆ፡፡
ዘመን አልፎ ዘመን ሲተካ
የአገሬ ጀምበር አምራ ስትፈካ
በማንነቱ ልጇ ሲመካ 
ከሺሕ ዘመናት ታሪክ ደክታ
እመር ስትል ዘመኑን ዋጅታ
መጠጊያ ሁና የሕዝቧ ዋልታ
ስደት ቀርቶላት ቸነፈር አልፎ 
የውርደት ካባ ወድቆ ተገፎ
ማየት እሻለሁ-በሞገስ ቁማ-ክብሯ ተሟልቶ
የተሰበቀው-የጠላት ደባ-ሴራው ተራቁቶ፡፡
ወንድወሰን ውቤ
ጳጉሜ 3/2007 ..



No comments:

Post a Comment