Tuesday, January 12, 2016

“ለድለላ” ሕወሃት ከፍተኛ የጦር አዛዥነት ሹመት ሊስጥ ነው! “እንዴት ጠባቦች ይጫወቱብናል?”



tplf generalsሕወሃት የከፍተኛ መኮንኖች “የመደለያ” ሹመት ለመስጠት ማቀዱ ተሰማ። አባይ ጸሃዬ ለህዝባዊ ተቃውሞው የተሰጠው መልስ የተለሳለሰ ነው አሉ። ህዝባዊ አመጹ ከቁጥጥሩ ውጭ መሆኑን ኢህአዴግ ይፋ አደረገ። ግርፋት፣ ግድያ፣ እስር፣ እንግልትና ስደት ያሳሰባቸው ስጋታቸውን እየገለጹ ነው።
የጎልጉል የአዲስ አበባ ዘጋቢ የመከላከያ መረጃ አቀባዮቹን ጠቅሶ እንዳመለከተው፣ በመከላከያ ሠራዊት ውስጥ አለመግባባቱና መቃቃሩ ከሯል። በሠራዊቱ ውስጥ የአንድ ብሔረሰብ አባላት ፈላጭ ቆራጭነት የፈጠረው ልዩነት መባባሱ አሁን ከተቀጣጠለው ህዝባዊ ቁጣ ጋር ህወሃትን አሳስቦታል። አርዶታል።
እንደ ዘጋቢያችን ገለጻ ኢትዮጵያን በተገንጣይ ስም እየመራ ያለው የትግራይ ነጻ አውጪ ግንባር (ሕወሃት) አሁን በኦሮሚያ ክልል የተነሳው ህዝባዊ እምቢተኛነት ወደ ሌላ ክልል እንዳይዛመት ሰግቷል። ለዚህም አንዱ የስጋት ማስተንፈሻ ተደርጎ የተወሰደው በመከላከያ ሠራዊት አመራሮች ዘንድ ያለውን ውጥረት “በመደለያ” ሹመት ማስተንፈስ ነው።
“የታቀደው ሹመት መደለያ ነው። የመጀመሪያ ተሹዋሚ ይሆናሉ ተብሎ የተያዙት ባብዛኛው የኦሮሞና የአማራ ልጆች ናቸው” በማለት መረጃውን ያቀበሉት ክፍሎች ሹመቱ እስከ ጄኔራልነት የሚደርስ እንደሆነ አመላክተዋል። የዜናው ምንጮች ሹመቱ ይፋ የሚሆንበትን ጊዜ መቼ እንደሚሆን ግን ሳይገለጹ ቀርተዋል። ሃሳቡ ከመቅረቡ ውጪ ውሳኔ ተሰጥቶበት ተግባር ላይ የሚውለው ቀን ያልገለጹት ምንጮች “አዲስ የሚሰጠው ሹመት ከሙሉ የኃላፊነት ነጻነት ጋር አይደለም” በማለት አስታውቀዋል።
“… የመከላከያ ሠራዊት አባላት የተገነባው በደሃ ልጆች ነው። እባካችሁን እንደናንተው የድሃ ልጆች ወገኖቻቹህን አትግደሉ። ተንደላቃችሁ የምትኖሩም ለዚህ ህዝብ ራሩለት። ለራሳችሁ ጥቅም ስትሉ ይህን ህዝብ አታስፈጁት … የድሃ ልጅ በድሃ ላይ እንዲዘምት መደረጉ ያሳዝናል” ሲሉ አቶ በቀለ ገርባ ለኢህአዴግ የመከላከያ ሰራዊት ጥሪ ማስተላለፋቸው አይዘነጋም። ለህወሃት ታማኝ አገልጋይ ሹመኞችም “አሁን በተያዘው መንገድ ከተቀጠለ ለማንም አይበጅም” ሲሉ በግልም ሆነ በጋራ ህዝብን የሚያከብር ታሪካዊ ውሳኔ እንዲወስኑ ተማጽነው እንደነበር የሚታወስ ነው።
ይህ በእንዲህ እያለ ከ140 ሰዎች በላይ የተገደሉበት ህዝባዊ ተቃውሞ ከቁጥጥር ውጪ መሆኑንን ኢህአዴግ አስታውቋል። የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር ጌታቸው ረዳ ለመገናኛ ብዙሃን ሲያስረዱ “ችግሩ ከቁጥጥራችን ውጪ ሆኗል። … አሁን በሟቾች ቁጥር የምንከራከርበት ወቅት አይደለም” ብለዋል። የኢህአዴግ አፈቀላጤ ጌታቸው መናገር በተሳነው አንደበት ይህንን ካሉ በኋላ አባይ ጸሃዬ ሰላማዊ ተቃውሞ ባሰሙ ኢትዮጵያዊ የኦሮሞ ተወላጆች ላይ የተወሰደው ርምጃ የተለሳለስ መሆኑንን ያስታወቁበት ሪፖርት ይፋ ሆኗል።
የኦሮሚያ ሚዲያ ኔትዎርክ ይፋ ባደረገው የአባይ ጸሃዬ ድምጽ “እየተወሰደ ያለው ርምጃ በቂ አይደለም። በክልልና በፌዴራል መንግሥት መልፈስፈስ ታይቷል” ሲሉ ተደምጠዋል። “እናንተ ደካሞች ናችሁ፣ ጠባቦች እንዴት ይጫወቱብናል?” በማለት ርምጃው የተለሳለሰ በመሆኑ ተጥናከሮ ሊቀጥል እንደሚገባ አሳስበዋል። ታህሳስ 20 ቀን 2015 ጎንደር ባንድ ሆቴል ውስጥ በተደረገው የኢህአዴግ ከፍተኛ አመራሮች ስብሰባ ላይ አባይ ጸሃዬ ሲዛለፉ ተሰምተዋል። ቀደም ሲል “ልክ እናስገባለን” ማለታቸውና ከመሬት ንግድ ጋር በተያያዝ “የመሬት ከበርቴው ሚኒስትር” እንደሚባሉ ጠቅሰን መዘገባችን አይዘነጋም። (“የመሬት ባላባቱ” ሚኒስትር!! በሚል ርዕስ ከዚህ በፊት ያተምነውን ዜና ከዚህ በታች ይገኛል)

No comments:

Post a Comment